Tuesday, August 12, 2014

ዋ! ወንድሜን!

ዋ! ወንድሜን!
ይድረስ ለወንድሜ “ለማላውቅህ”፣ ባረመኔ ገራፊዎች እጅ ለወደቅኸው፣
በኮረንቲ ሽቦ ገመድ - መላው አካላትህ ለሚላጠው፤
ከጭለማው የግፍ “ቻምበር” - ከሰቆቃ መፈጸሚያው፣
የስቃይህ ጣር ዋይታ - ላለም ጆሮ ለተሰማው።
ከህመምህ ስታገግም - ላንዲት ቅጽበት ብጠይቅህ፣
ምንስ ይሆን “ሃጢያትህ”? በነሱ ዐይን “ጥፋትህ”?
እኔማ ምን አውቄ?
ስቃይህን ሰምቼ እንጂ መጨነቄ፤
ግን፣ ግን...፣
ከሚያቃትተው ድምጽህ ዋይታ፣
እስኪ ልገምት ...”መላ-ልምታ”፣
(በመዝገበ-ማሕደር ተከትቦ- ዓለም የሚያውቀውን እውነታ)፤
...ቆዳህን ባኮርባች ሲልጡ - ስጋህን በብረት ሲያቃጥሉ፣
 አጥንትህን ፍቀው ሲግጡ - በስ ብልት ጠርሙስ ሲያንጠለጥሉ፣
 አደንዛዥ መርፌ እየወጉ - መርዛቸውን በህዋሳትህ ሲረጩ፣
 በቀዝቃዛ ውሃ እየደፈቁ - ከደረቅ ግድግዳ ጋር ሲያጋጩ፣
 ጥፍርህን እየነቀሉ - ጸጉር-ጺምህን ሲነጩ...፣
 በፈላ ዘይት እየጠበሱ፣
 ዘቅዝቀው በመስቀል እንቅልፍ እየነሱ፣
 የጸያፍ ስድብ ውርጂብኝ - የጭለማ ክፍል ደባ፣
 የአእምሮ ስቃይ በትር - የስነ-ልቦና ሰለባ...፤
 ለምኑ ይሆን የተጨነቁ? - አሰቃይቶ “ቃል” ለመቀበል?
“መረጃ” ለማሰባሰብ? - “ፍርድ ቤት” የሚቀርብ ለይምሰል?
እንደዚያማ እንዳልገምት - ፍርድ ቤቱ በጃቸው፣
በቀጭን ትዕዛዝ የሚወስኑ - ፍርደ-ገምድል ዳኞቻቸው፤
እና ታዲያ ለምን ይሆን? በሰው ልጅ ገላ እንዲህ መጨከኑ፣
ያገር-ልጅ በወንድሙ ላይ - ጭራቅ፣ አውሬ መሆኑ?!
… ቀውስ ነው ቂም-በቀል - ያገር-ወዳድ ቅስም ለመስበር፣
በዘረኝነት ጎዳና - ዝንተ-ዓለም ለመዘወር፤
እኩይ መንፈስ ጥላቻ ነው - የበታቸኝነት ስሜት ሕመም፣
ባለም መድሃኒት እማይድን - ነቀርሳ እማይታከም፤
ይድረስ ለወንድሜ “ለማላውቅህ” - ለእምዬ ልጅ የአንዷ፣
ለጋራ እናታችን፣ ለእማማ ኢትዮጵያ ስትል እምትቀበል ፍዳ፣
እግዚአብሔር ጽናቱን ይስጥህ - ከበላዔ-ሰብ መንጋጋ አላቆ፣
ለመልካሙ መጪ ጊዜ ያብቃህ - የተሰቃየህላትን ሀገር ጠብቆ!

ጌታቸው አበራ
ነሐሴ 2006 ዓ/ም
 (ኦገስት 2014)
ማስታወሻነቷ፦

1.ወያኔ ለፕሮፓጋንዳው ፍጆታ ሲል፣ በኢቲቪ አቅርቦት በነበረው የአቶ አንዳርጋቸው ጽጌ ቪዲዮ ቅንብር
 ሁለተኛው ክፍል ላይ፣ ከምስሉ በስተጀርባ (ባክ ግራውንድ)ይሰማ ለነበረው የሰቆቃና የስቃይ ደምጽ!

2.በዚሁም መነሻነት፦ ፍትህ፣ እኩልነትና ነጻነት... በሃገራችን እንዲሰፍኑ በመታገላቸው ብቻ፣ የወያኔ ማሰቃያ እስር-ቤቶች
 ውስጥ፣ ፍጡር ከሚችለው በላይ የሰቆቃ ግፍ ለሚፈጸምባቸው ኢትዮጵያውያን ወገኖቼ በሙሉ!

No comments:

Post a Comment